Saturday, May 12, 2012

http:///? www.meleket4u.blogspot.com/

Thursday, May 10, 2012


ማን አሸነፈ?

በቤተክርስቲያን አሸናፊ አይኖርም ብሎ መረዋ የጻፈው ከ ፫ ዓመት በፊት ነበር። መረዋ ዛሬም ማንም አሸናፊ አይደለም ብሎ ያምናል። እንዴውም የገደለው ባሌ የሞተው ወንድሜ የሚለውንም እንደ ምሳሌ መጠቀሙን ያስታውሳል። እንሆኝ የቤተክርስቲያናችን ውጣ ውረድ ከተጀመረ ከ ፬ ዓመት በላይ ሆኗል።
ይህ ሁሉ ውጣ ውረድ ይህ ሁሉ ክስ የመጣው ደግሞ ከሳሾች ገንዘብ ፈልገው አልነበረም።
ቢሆንማ ኖሮ ካሳ በጠየቁ ነበር።
ለስልጣን ብለውም አልነበረም።
ቢሆንማ ኖሮ ምእመን ሳይወያዩበት በቦርዱ "ጸደቀ" የተባለው መተዳደሪያ ደንብ ለተመራጭ አስተዳዳሪዎች የፈላጭ ቆራጭ ስልጣን የሚሰጥ ነበር።
ለንብረትም አልነበረም።
ቢሆንማ ኖሮ የንብረት ክስ ከተመሰረተ ፍርድ ቤቱ ያገባዋልና ይወስንላችኋል ሲባል የንብረት ክስ አንመሰርትም ባላሉ ነበር።

ነገሩ የመብት ጉዳይ ሆነና ይኸው እስካሁን እያወዛገበ ይገኛል። ለስለሰብአዊ መብት እንከራከራለን የሚሉ ግለሰቦችና ድርጅቶች መብት እንንፈግ ብለው ሲዶልቱ መክረማቸውን ያያችሁት ጉዳይ ነው ። በመብቴ አልደራደርም ያለው አባል ከአባልነት እራሱን እያሸሸ ለመምጣቱ ደግሞ ምስክር መጥራት የሚያስፈልግ አልመሰለንም። ምስክሩ እናንተ ናችሁና።

፴ ብር ለይሁዳም አልበጀምና ተው ሲባል ሰሚ አልነበረም። ይህ ግን ቤተክርስቲያኑን አደኸየ እንጂ አልጠቀመም።
አቶ ኃይሉ እጅጉ በመሰረቱት ቤተክርስቲያን አዳራሽ ለመብት ቆመሃልና አትገባም ሲባሉ የዓይን ምስክር ነበርን። ነበራችሁ።
አቶ ሙላው ወራሽ እንደ ወረደባቸው አሉባልታና የስም ማጥፋት ዘመቻ አገር ለቀው ይወጣሉ ብለው የጠበቁ ቢኖሩ የሚያስገርም አልነበረም።ያ ግን አልሆነም።

ደጋፊም ተቃዋሚም አሁንም አንድላይ ነን። አሁንም አንድ ላይ እያስቀደስን ነው ማለት እውነት ነው። ጸሎታችንን እኩል ይሰማል ማለት ግን አጠያያቂ ይሆናል። ትላንት ከአዳራሽ ያስወጡ የነበሩ እራሳቸው እንደወጡ ያያችሁት ነውና መድገም አያስፈልግም።

ሰባት ጊዜ ሽማግሌ አናግረናል የሚሉት የመብት ተከራካሪዎች፡ ሰባቱንም ጊዜ ከሽማግሌዎች ጋር በአክብሮት ተወያይተን ተለያይተናል ብለው በልበ ሙሉነት ይናገራሉ። በምስጋና የተለያዩት የመብት ተከራካሪዎች፣ የሚኮሩበት ጉዳይ ቢኖር ሽማግሌዎቹን ማሳመን መቻላቸው ብቻ ሳይሆን ከመሃከላቸው ደጋፊና አብሯቸው የሚታገል ማትረፋቸው ነው። የዛሬ ሳምንት በቤተክርስቲያን የቦርድ መሰብሰቢያ አዳራሽ በመገኘት ሁለቱም ወገኖች ታረቁ ተብሎ ሲነገር ሕዝቡ እልል ሲል ያየ ቢያለቅስ ምን ይፈረድበታል? ሁኔታው ግን ሰዓታትም ሳይቆይ እርቅ ፈርሷል ተባለና ተቀየረ። ማን እንዳፈረሰው ደግሞ ሽማግሌዎቹን መጠየቅ ይሻላል እንላለን።

የመብት ታጋዮቹን ደገፋችሁ በሚል የወሲብ አሉባልታ የተነዛባቸው ጠነከሩ እንጂ ሸብረክ ሲሉ አላየንም። ባልሰሩት የነፍስ ግዳይ የተወነጀሉት አሁንም እስር ቤት ገብተው አላየንም። ከመብት ተከራካሪዎቹ ቃለ አባባል እንውሰድ " እኛ የእምነትና የእውነት ድሃ አይደለንም" የሚል ነው። ፍርድ ቤት ይለየን እንደተባለው እነሆ ፍርድ ቤት እየለየው ነው። ማሸነፍን ግን አላየንም።

ውድ አንባብያን ፍርድ ቤቱ በዛሬው እለት የቦርድ አባላት ከሳሾችን ከዓመት በፊት ከቤተክርስቲያን እናባራችሁ ብለው በወሰኑባቸው ማግስት አታባርሩንም በሚል ስማቸው ተካቶ ከነበረው 28 ተባራሪዎች ውስጥ የሆኑ ምእመናን ክስ መመስረታቸው ይታወሳል። በመሆኑም የነበረውን በየጊዜው የፍርድ ቤት ውሎ መረዋ በወቅቱ የዘገበው ጉዳይ ነበርና ዛሬ ወደ ኋላ ተመልሶ ሁኔታውን በመተንተን ጊዜአችሁን ከመሻማት ይቆጠባል። ነገር ግን የዛሬ ዓመት ክሱን እናቁም በማለት ከሳሾች ከደጋፊዎቻቻው ጋር በመስማማት ክሱን ቢያቆሙም ቦርዱ እስከዛሬዋ የፍርድ ሰዓት ድረስ ለጠበቃ ያወጣንውን 89,000 ብር ይክፈሉን ሳይከፍሉን ክስ አናነሳም ብለው ሲከራረሩ ቆይ ተው ነበር። በዚህም መሰረት በዛሬው እለት ዳኛው የዚህን ክርክር የመጨረሻ ውሳኔ በመስጠት ገንዘብ መጠየቅ አትችሉም ብለው ብይናቸውን ሰጥተዋል። ይልቅስ ይላሉ ዳኛው ይህንን የእምነት ጉዳይ በቤተክርስቲያን ደንብ በውስጥ ለመፍታት ብትሞክሩ መልካም ነው። በማለት ምክራዊ ብይንም ሰጥተዋል። ከሳሾች ለቦርድ አባላት ፩ ብር (አንድ ብር) እንዲከፍሉ እንደተወሰነባቸው ደግሞ የነገሩን የመብት ተከራካሪው ቡድን አባል ለዚህ ምእመናንን እርዳታ አንጠይቅም በማለት እየሳቁ ነበር።

ይህ ቦርዶቹ የሚጠይቁት የጠበቃ ገንዘብ ባለፈው አወጣን የሚሉትን ከ140,00 ብር በላይ የሆነውን አያጠቃልልም። በቅርቡ መረዋ የደረሰውን የቦርድ አባላት ባለፈው ፩ ዓመት ተኩል ለጠበቃ ከፈልን ብለው ፍርድ ቤት ያቀረቡትን የ 89,000 የወጭ ሰንጠረዥና ከሳሾች በሁለት ዓመት ለጠበቃ ከፈልን የሚሉትን 21,593 ብር የወጭ ሰንጠረዥ ያጠቃለለ በገጹ ላይ እንደሚያትም ቃል ይገባል። ከየትም ይሁን ከየት ማንም ከፈለው ማ ከፋዩ የቤተክርስቲያናችን አባላት ያዋጡት ገንዘብ ነውና። ለአባላት ይጠቅም ዘንድ በእጃችን ያለውን ማናቸውንም መረጃ እንዳስፈላጊነቱ ለማሳወቅም እንደምንጥር ሰንናገር በእርግጠኝነት ነው።

ለመንፈሳዊ አባቶች ያለንን አድናቆትና አክብሮት እየገለጽን የኛን ወገን ዜና ማሰራጫ ሌላ መድረክ ስለሌለን ይህንን የመተንፈሻ ገጽ መጠቀማችንን እንዲረዱልን እንወዳለን።

ውድ ምእመናን ከኛ ወገን የሚተላለፍ መልእክት አለን

ከጎናችን ሆናችሁ ለከረማችሁ፣ ለእውነት ስለቆማችሁ፣ ለተሰደባችሁ፣ ለተባረራችሁ፣ ሁሉ ሚካኤል ዋጋችሁን ይክፈላችሁ እንላለን። እኛና እናንተ እንቅልፍ ተኝተን እናድራለን እንቅልፍ ያጡ ሌሎች ናቸው።
እኛና እናንተ በእሳት ተፈትነን የሕይወት ጓደኛ ሆነናል።
በየወንዙ የሚማማሉት ሌሎች ናቸው።
እኛ ትናንትናም ዛሬም ትክክል ነበርን፣ ለሰላምና ለአንድነት ታግለናል።
አቋማቸውን እንደጥላ የማያምኑት ሌሎች ናቸው።

ሚካኤል ፍርድ እየሰጠ ነው። ለክፋት በቆመው ላይ የዘላለም ፍርድ ይስጥ።

እኛ ማንንም አንጠላም ለሚጠሉን እንጸልያለን።
በማንም ላይ አንፈርድም፣ በሚፈርዱ እናዝናለን።
ማንም ከስራ እንዲወጣ አንፈልግም፣ ይህን ለሚያስቡ ሱባኤ እንገባለን።
በማስፈራራት አንፈራም ከጥል ይልቅ ለፍቅር እንሰግዳለን።
ቤተክርስቲያናችን እንደሚኖር እኛ ግን እንደምናልፍ እናምናለን።
ቤተክርስቲያን የአባቶችና የክርስቲያን ስብስብ እንጂ ሕንጻና ገንዘቡ ነው ብለን ለደቂቃም አናምንም።

ለሰላም እንጸልይ።

እንኳን ደስ አለን።

8 comments:

  1. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ምዕመናን ዓለም አቀፍ ማኅበር WORLD ASSOCIATION OF PARISHIONERS OF E.O.T. CHURCH

    የዕርቀ ሰላም መታጣት፤

    በጎ ጎን ምን አለው?
    • አብረው መሰብሰባቸውና መቀደሳቸው በጣም ጥሩ ነው።
    2. መጥፎ ጎን አለው?
    • ሀ. ውግዘቱ አለመነሳቱ
    • ለ. ዕርቀ ሰላሙ አልወረደም
    3. ምን እናድርግ?
    • ሀ. በዓለም አቀፍ ደረጃ ፀሎት እንዲደረግ
    • ለ. የካህናትንና የምዕመናንን ተፅኖ እንዲጠየቅ
    • ሐ. አንድ ጠንካራ መግለጫ እንዲወጣ ማድረግ
     ሦስት ጊዜ ተሰብስበው ውግዘቱ አለመነሳቱና ዕርቀ ሰላሙ አለመውረዱ ምዕመናንን እጅግ ያሳፈረና ያሳዘነ መሆኑን።
    4. ዕርቀ ሰላሙ አለመውረዱ የሚያስከትለው ጠንቅ፦
    • ሀ. የአጽራረና የሌላ ኃይማኖት መጠናከር
    • ለ. ለደብሮች፤ ለገዳማት፤ አብነት ትምህርት ቤቶች እርዳታ መቀነስ
    • ሐ. የምዕመናን ተሳትፎ ቁጥር መመንመን / መቀነስ
    • መ. ዴር ሱልጣን ያለው ገዳም ድጋፍና በቂ ትኩረት አለማግኘት
    5. አማራጭ፦ የእህት ቤተክርስቲያን አባቶችን እርዳታ መጠየቅ፦(ተቃዋሚም ሊኖር ይችላል)
    (ማለት፦ የግብፅ፤ የሶርያ፤ የህንድ፤ የአርመን ናቸው)

    ReplyDelete
  2. ሰላም የሚፈጠረው ሰላም ብሎ በመነሳት ብቻ ነው።
    ሰላም የሚፈጠረው ሰላም ብሎ በመነሳት ብቻ ነው።





    ሁሉንም ቻይ አምላክ እንደየሥራችን የእጃችንን ይከፍለናል ማለት እውነት መሆኑ ባይካድም ምሕረቱ የማያልቅበት እየሱስ ክርስቶስ አብሮት የተሰቀለውን ነፍሰ ገዳይ እንደማረ ሁሉ እኛንም በምሕረቱ ይዳስሰናል ብለን እናምናለን። ደካሞች ነንና ጥንካሬን፣ ፈሪዎች ነንና ድፍረትን፣ ንፉግ ነንና ቸርነትን፣ ቂመኞች ነንና ይቅርታን፣ ከሀዲዎች ነንና እምነትን፣ እንደሚቸረን ደግሞ ደጋግሞ የተነገር በመሆኑ የቃሉ ፍጻሜ ላይ መጠራጠር ከሌለ በስተቀር ይሆናል ያለው እንደሚሆን በሙሉ እምነት መናገር ይቻላል።
    አዞ አፉን ከፍቶ በመተኛቱ የሞተ እየመሰላቸው የሚጠጉትን እንደሚያድን ሁሉ የፈጣሪን አምላክነት የሚፈታተኑትን በመንግሥቱ ቀናዊ ነውና እንደሚገስጻቸው ደግሞ ለዘመናት ያየነው ያስተዋልነው በመጽሐፍ ያነበብነው ነው።
    ይህንን ካልን በኋላ ሰሞኑን በዚህ በዳላስ የተደረገውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የሰላም ጉባኤ በጉጉት ከጠበቁትና በመጨረሻም በውጤቱ ከተበሳጩት መሃል እራሳቻንን እንደምራለን። ሰላም ወረደ ማለት የሁሉም ጊዜ እምነትን በማስፋፋትና በማጠናከር ላይ እንጂ በማፍረስ ላይ አይሆንም ከሚል አመለካከት። የመንፈሳዊ አባቶች ሱባኤና ጸሎት፣ የምእመናን ለቅሶና እግዚኦታ ምላሽ ያገኝ ይሆናል ከሚልም መንደርደሪያ በመነሳት ነበር።
    ለምን አልሆነም ለሚለው የበኩላችንን መናገር እንችላለን። ዋንኛውና የማንጣላበት ግን እሱ ስላልፈቀደ ብቻ ነው። ከሃገር ቤት የመጡ አባቶች ግዝትን አንስተው እዚህ ያሉትን መንፈሳዊ አባቶች ስልጣን ተቀብለው ከነክብራቸውና ከነማእረጋቸው እንዲገቡ መስማማታቸውን ሲቀበሉ፣ በስደት ያሉ መንፈሳዊ አባቶች ግን ለ 20 ዓመት ሲያነሱት የኖሩትን የመንበረ ስልጣን ጥያቄ አሁንም የሙጥኝ ማለታቸው ግን ሁላችንንም አሳዝኖናል።
    ክርስቶስ እንደሚገደል እያወቀ ወደ መሰቀያው የሄደው እኮ መሰወር አቅቶት አልነበረም። የሰቀሉትን ግፈኞች የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው ያለው መቅጣት ተስኖት አልነበረም። የተሰቀለው በደሙ ከሃጥያታችን ሊያነጻን ይቅር ያለው ምህረትን ሊያስተምረን ነው እንጂ። ለሐዋርያት ስልጣን የሰጠውም እንደኔ ሆናችሁ አስተምሩ በስሜ ወንጌልን ስበኩ ህሙማንን ፈውሱ አርአያም ሁኑ በማለት ነው። ታዲያ አባቶች ለዚህ መንፈሳዊ ስልጣን ያበቃቸውን አምላክ በተሰበጣጠረው ምእመን ችግር መፍትሄ እንጂ መለያያ ባይሆኑ እንዴት መልካም ነበር። መቼም እድሜ የማይደበቅ ስጦታ ነውና ለመጠራት የቀረን ስንት ጊዜ ይሆን ብሎ መጠየቅም መልካም ነው። ሰላምን ለሚፈልግ ምእመን ሰላም ለክሙ ማለት እንጂ መለያየትን እንዴት ለማሳለፍ ይፈለጋል። ተአምር የሚገለጽባቸው ገዳማት ደግሞ ያሉት ሃገር ቤት ነው ብለን እንቀበላለን። ያ የሆነው በየጥሻው በየዋሻው፣ በየሰቀላው፣ በየዱር ገደሉ ተጠልለው በሚጸልዩ መነኮሳትና አበው እንደሆነ እናምናለን።
    ስለሆነም ዛላለማዊ ስፍራን እንጂ ጊዚያዊ ወንበርን በመተው ለሰላም እንዲነሱ እንለምናለን። ፈጣሪያችን የኢትዮጵያን ለቅሶ ሰምቶ ምህረቱን ይላክ።

    ReplyDelete
  3. ምን ዓይነት ለውጥ ለቤተ ክርስቲያን? (ለግልጽ ውይይት የቀረበ)
    ማውጫ፦ ሐተታ Posted by DejeS ZeTewahedo
    በትዕግስት አንብቡት፤ ሚዲያዎችን ጨምሮ ለአባቶችም ለምእመናንም በማድረስ ተባበሩን። .
    (ደጀ ሰላም፤ ሰፕቴምበር 3/211 READ IN PDF)፦ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ጨርሶ መደበቅና ማስተባበል እንኳን ከማይቻልበት ደረጃ የደረሰው የቤተ ክርስቲያናችን ውስጣዊ ቀውስ እጅግ አሳሳቢ ሆኗል። እንደ አንድ የቤተ ክርስቲያኒቱ ተከታይ ነገሩን በተቻለን ቅርበት ስንከታተል ቆይተናል። በየሚዲያው የሚወጡትን ጽሑፎች፣ ዜናዎች እና ቃለ ምልልሶችንም ሳያመልጡን ለመረዳት ሞክረናል። ሆኖም በሚዲያ የሚቀርቡት ብዙዎቹ አስተያየቶች ችግሩን በተረዱት መጠን ወይም መልክ በማንጸባረቅ ላይ የተወሰኑ ናቸው።
    ችግርን በትክክል መረዳት የመፍትሔው ግማሽ እንደመሆኑ ውይይቱ የሚወደድ ነው። የመፍትሔ አቅጣጫ ለማመላከት የሞከሩ ፀሐፊዎችና ተናጋሪዎች ቢኖሩም ቅሉ ብዙውን ጊዜ ሐሳቦቹ ቅንጭብ በመሆናቸው አጠቃላይ ውጤታቸው በግልጽ የሚታይ አይደለም። ከሁሉም በላይ የሚያሳዝነው ደግሞ ቤተ ክርስቲያኒቱ የራሷን ችግር የምትመረምርበት ተቋማዊ ዝግጅት የሌላት ሆና ትታያለች። ምእመናንና ሌሎች ተቆርቋሪ ዜጎችም ተጨባጭ ለውጥ ሊያመጣ የሚችል አስተዋጽዖ የሚያደርጉበት ዕድል ዝግ ነው ማለት ይቻላል።
    እነዚህ ችግሮች ሲያብሰለስሉን ቆይተዋል። ችግሩ ከቁጥጥር ውጭ ከመሆኑ በፊት በየደረጃው በአስቸኳይ ቀጥተኛና ጥልቅ ውይይት መደረግ እንዳለበት እናምናለን። እንደ ዜጋ፣ ከዚያም በላይ እንደ አንድ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጅ የራሳችንን ሐሳብ ለማካፈል ቀርጠን ስንጽፍ የቆየነው ከዚህ በመነሣት መሆኑን በተደጋጋሚ መግለጻችን ይታወሳል። ይህን ሐሳባችንን ሌሎች ሚዲያዎችም እንደሚያስተናግዱት ተስፋ እናደርጋለን። ወደ ሐሳቡ ከመግባታችን በፊት ሦስት ነገሮችን በማሳሰቢያ መልክ መግለጽ እንወዳለን።
    1. አሁን የምንደብቀው፣ ብንደብቀውም የሚጠቅመን ገመና የለም። የቤተ ክርስቲያንን ችግር በግልጽ አውጥቶ መነጋገር ገመና እንደመግለጥ የሚቆጠርበት ጊዜ አልፏል። ችግሩን ለመረዳት፣ መፍትሔ ለመፈለግ እስከጠቀመን ድረስ ማናቸውንም ነገር በግልጽ መጥቀስ እንደበጎ ሊታይ ይገባዋል ብለን እናምናለን። እንደተለመደው በመሠረታዊው ችግር ላይ ሳይሆን በእንጭፍጫፊ እና ሁለተኛ ደረጃ እንከኖች ላይ ጉልበታችንን፣ ጊዜያችንን አናባክን።
    2. የቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊና መንፈሳዊ ችግር እኛ ሰዎች የፈጠርነው ችግር ነው። ስለዚህ ችግሩን የመፍታት ቀዳሚ ኃላፊነት ያለብን እኛው ነን። በዚህ ዓላማችን እግዚአብሔር እንዲረዳን እንማጸናዋለን፣ ያለጥርጥርም ይረዳናል። ነገር ግን ቤተ ክርስቲያን አሁን የገባችበት ቀውስ የእግዚአብሔር ፈቃድ እንደሆነና የእኛ ጥረት ለውጥ እንደማያመጣ ማሰብ በሰውም፣ በታሪክም ይሁን በፈጣሪ ፊት ከኃላፊነት የሚያድነን አይሆንም። ስለዚህ ነገሩ የግልና የጋራ ኃላፊነታችንን የመወጣት ኅሊናዊና አገራዊ ግዴታ ነው።
    3. አንዳንድ ሰዎች አሁን እየታዩ ያሉትን ችግሮች አምኖ ተቀብሎ ስለ መፍትሔ ከመነጋገር ይልቅ እጅ በመጠቋቆም ወይም በጥንታዊቷ ቤተ ክርስቲያን የነበሩ ጠንካራ ተሞክሮዎችን ብቻ በማንሣት የራሳቸውንም የአድማጮቻቸውንም ትኩረት ሲያባክኑ ይታያል። እነዚህን ሰዎች “ታሪክ ውስጥ ከመደበቅ ወጥታችሁ እውነትን ተጋፈጡ፤ እጅ መጠቋቆሙ ለውጥ አያመጣም” ልንላቸው ይገባል። አሁን የተረት ጊዜ አልፏል። አሁን ያለችውና የምንነጋገርባት ቤተ ክርስቲያን በተቋማዊ ቅርጿ ከጥንታዊቷ የተለየች ናት። በቀደመው ዘመን የነበረ ጥሩ ነገርም ለአሁን ችግር መቅረፊያ ትምህርት እንጂ የአሁኑን መሸፈኛ ወይም ማረሳሻ ሆኖ መቅረብ የለበትም። እንዲህ ማድረግ አሁን ያለው ችግር እንዲባባስ ጊዜ መስጠት ነው።
    ለውይይት እንዲረዳን በአራት ጭብጦች ላይ እናተኩራለን። የችግሩ ተቋማዊ አድራሻ፣ የችግሩ ምንጭ፣ ያለው ችግርና የሚያስከትለው አደጋ፣ ምን ዓይነት ለውጥ እንደሚያስፈልገን ማለትም አዝጋሚ ወይስ አብዮታዊ? የሚሉትን ጭብጦች እናነሣለን። በሚገባ የሚታወቁ ችግሮችን ወደመዘርዘር ሳንገባ እያጠቃለልን ለማቅረብ እንሞክራለን። በዚህ ጽሑፍ ውስጥ ሙሉ በሙሉ ያተኮርነው በውስጣዊ ችግሮች ላይ ብቻ ነው። ግምገማውን የተሟላ ለማድረግ ውጫዊ ሁኔታዎችና ተጽዕኖዎች እጅግ አስፈላጊ እንደሆኑ እንረዳለን። ሁሉንም ነገር በዚህ አጭር ጽሑፍ ማጠቃለል ግን የሚሞከር አልሆነልንም። ውስጣዊውንም ቢሆን በጨረፍታ ነው።
    ውይይታችንን ለመጀመር ብዙ አማራጮች አሉን። የችግሩን መጠን፣ በማስከተል ላይ ያለውን ጉዳትና ያዘለውን አደጋ መተንተን የበለጠ ተገቢ ይመስለናል። የምንመርጠው የመፍትሔ አቅጣጫም በዚህ ላይ የተመሠረተ ይሆናል። በችግሩ ስፋት፣ ባሕርይ እና አደጋ ላይ ተቀራራቢ ግንዛቤና አቋም ካልያዝን በመፍትሔዎቹ ላይ መስማማት አንችልም። እዚህ ላይ በሁሉም ላይ ፍፁም አንድ ዓይነት መረዳትና መግባባት መፍጠር አለብን። ሙሉ በሙሉ ግን ይቻላል ማለታችን አይደለም።
    የችግሩ ተቋማዊ አድራሻ
    አሁን ቤተ ክርስቲያንን እንደጎርፍ ያጥለቀለቁትን ችግሮች በተቋማዊ አድራሻቸው ብንመድባቸው ስምንት ዋና ዋና ቦታዎችን እናገኛለን። እነዚህ ተቋማት እንደየደረጃቸው ቁልፍ የአመራር እና የአፈጻጸም ሚና የሚጫወቱ ናቸው። ያለእነዚህ ተቋማት የቤተ ክርስቲያኒቱን ተቋማዊ ሕይወት ማሰብ አይቻልም። የአንዱ በሽታ የሌላውም ሕመም ነው፤ የአንዱ መዳከም ለሌላው ውድቀት በር ከፋች ነው። ተቋማቱ በዓላማቸው፣ በሥራ እሴቶቻቸው እና በራዕያቸው አንድ ዓይነት እንደሆኑ ይታመናል። ወይም የአንድ ቤተ ክርስቲያን ልዩ ልዩ ብልቶች እንደመሆናቸው መጠን እንደዚያ እንዲሆኑ ይጠበቃል። አስቸኳይ ትኩረትና መሠረታዊ ለውጥ የሚፈልጉት ተቋማቱ የሚከተሉት ናቸው።
    1. ቅዱስ ሲኖዶስ፣
    2. ቅ/ ፓትርያርኩ፣
    3. ጠቅላይ ቤተ ክህነት፣
    4. አኅጉረ ስብከት፣
    5. አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት አስተዳደር፣
    6. ሰበካ ጉባኤ፣
    7. ማኅበረ ካህናት እና
    8. ሕግጋተ ቤተ ክርስቲያን፣
    ስለ እነዚህ ተቋማት ዝርዝር ድክመት መጻፍ ሰፊ ቦታ የሚወስድ ነው። አብዛኛውም ተደጋግሞ የተነገረ ነው። ቀዳሚዎቹን ሰባት ተቋማት አስተሳስረው የሚይዙት መጠባበቂያዎች ሕግጋት ናቸው። ሕግጋት ስንል በተለይ አስተዳደርን፣ የአስተዳደር ዘይቤን የሚመለከቱትን ነው። አሁን ከሰፈነው ዝብርቅርቁ የወጣ የሚመስል፣ ጠያቂና ተጠያቂ የማይለያዩበት፣ የዕውቀትና የሥራ ጥራት መለኪያ ደብዛው የጠፋበት ሁኔታ በመነሣት የችግሮቹ አንዱ ምንጭ ከሕግጋትና ከአፈጻጸማቸው ጋር የተቆራኘ እንደሆነ አያጠራጥርም። (ሕግጋትን እንደ አንድ “ተቋም” መመልከት በማኔጅመንትም ይሁን በኅብረተሰብእ ሳይንስ የተለመደ ነው።) እዚህ ላይ በሥራ ላይ የሚገኘው ቃለ ዐዋዲም ይሁን ሌሎች መመሪያዎች/ ሕጎች ከነድክመቶቻቸውም ቢሆን በተግባር ላይ አልዋሉም። አንድ ሕግ ተግባር ላይ ሊውል ካልቻለ ሕጉ ራሱ ችግር ሊኖርበት እንደሚችል አመላካች ነው። ችግሩ “የአፈጻጸም ነው” ማለት ወደ ምን ዓይነት የስሕተት አዙሪት እንደሚከት ከኢሕአዴግ መማር ይቻላል።
    ይቀጥላል.... በሚቀጥለው ገጽ.....

    ReplyDelete
  4. ...ካለፈው ገፅ የቀጠለ....


    ለመሆኑ እነዚህ ችግሮች የደቀኑብን አደጋ ምንድን ነው? በእኛ አስተያየት፣ በአደጋዎቹ ላይ የሚኖረን አመለካከት የቤተ ክርስቲያናችንን መጻዒ ዕድል ሊወስን የሚችል ነው። እንዲሁ ለውይይት ያህል አሁንም አንኳር የምንላቸውን አደጋዎች እንዘርዝር። አንዳንዶቹ አደጋዎች ከወዲሁ መድረስ መጀመራቸውን ልብ ይሏል።
    1. የቤተ ክርስቲያኒቱ መሠረታዊ የሃይማኖት ትምህርት ሊፋለስ ይችላል፤ ይህም ለውስጣዊ የሃይማኖት አንጃ (የመናፍቃን ቡድን) መፈጠር በር ይከፍታል፣
    2. የቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ ማዕከላዊነት ሊናጋ ይችላል። (አጥቢያዎች፣ ወረዳዎች እና አህጉረ ስብከቶች በማዕከሉ ማለትም በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ አልመራም በሚሉ ቡድኖች እጅ ሊወድቁ ይችላሉ። ልዩነቱ በጳጳሳት ዘንድ መድረሱን፣ የጳውሎስ የመርቆርዮስ መባል መጀመሩን ልብ ይሏል። ሌላስ ሊከተል አይችልምን? )፤
    3. ቤተ ክርስቲያን በብሔር እና በፖለቲካ ልትከፋፈል ትችላለች (አልደረሰም ለማለት ያስደፍረናል?)፤
    4. ቤተ ክርስቲያን ጠብቃ ያቆየቻቸው ጠቃሚ ትውፊቶች፣ ቅርሶች እና ታሪኮች ያለ ባለቤት ይቀራሉ፤ የወሮበላ መነገጃ ይሆናሉ። ይህም ከተጀመረ ሰንብቷል።
    5. ልዩነቶቹ ወደ ምዕመናን ሊወርዱ ይችላሉ። ይህም አደገኛ ግራ መጋባት ይፈጥራል። ችግሩ ለአገርም ሊተርፍ ይችላል።
    6. ቤተ ክርስቲያኒቱ በአገሪቱ ውስጥ ያላት ተደማጭነት፣ አስተዋጽዖ እና ክብር ጠፍቶ ለአሸማቃቂ የሐፍረት ታሪክ መልስ ለመስጠት የምንገደድበት ሁኔታ ይመጣል። ከዚህ ከፊሉ መፈጸሙን ልብ ይሏል።
    7. ከሁሉም በላይ ደግሞ (እግዚአብሔር አይበለው እንጂ) የቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ ሕይወትና ክብር ይወድቃል፤ እነዚህን ማስቀረት ካልተቻለ ፈጣሪም፣ ታሪክም፣ አገርም፣ ልጆቻችንም ተባብረው እንደሚወቅሱን ቅንጣት ያህል አንጠራጠርም። እግዚአብሔር ይህንን ለሰው የማይቻል የሚመስለንን ውድቀት አሸንፈን የምንወጣበትን ጥበብ፣ ትዕግስትና እምነት እንዲሰጠን ዘወትር እንጸልያለን።
    ደጀ ሰላማውያን፣ አንባቢዎች ከእኛ በበለጠ የሚያውቁትን የችግር በመዘርዘር ሐዘን ውስጥ ከትተናችሁ እንዳንሔድ ስለመውጫውም የምናስበውን እናካፍል።
    ምን ዓይነት ለውጥ፤ አዝጋሚ ወይስ አብዮታዊ?
    ቤተ ክርስቲያን ለውጥ አያስፈልጋትም የሚል ሰው የሚገኝ አይመስለንም። ካለም እኛ የምንጽፈው ለእርሱ አይደለም። እሱ በምቾት እንቅልፉ እንዲቀጥል እንተወዋለን። “ፕሮቴስታንታዊ-ተሐድሶ” የሚባለው ፕሮጀክትም የእዚህ ጽሑፍ ዓላማ አይደለም። ከፍ ብሎ የተጠቀሱት ችግሮች ሲቀረፉ “ተሐድሶ” የሚባለው ነገርም ዘላቂ መፍትሔ ያገኛል። አሁን በአጽንዖት መጠየቅ የምንወደው የሚያስፈልገው ለውጥ ምን ዓይነት ነው? የሚል ነው። ከብዙ ሰው ጋር ስንወያይ - ከጳጳሳትም ከምእመናንም ጭምር ብዙዎች የአፈታቱን አቅጣጫና ፍጥነት ሳያስቡበት እናገኛቸዋለሁ። በደምሳሳው ግን አዝጋሚ የሆነ የችግር አፈታት ሒደት የሚመርጡ ናቸው። ሲፈሩም ይታያሉ። “አዝጋሚ ለውጥ ስንት ዓመት የሚፈጅ ነው?” ሲባሉም ቁጥር መናገር ይከብዳቸዋል። በእኛ አመለካከት ደግሞ የችግሩ ስፋት፣ ጥልቀት እና የሚያስከትለው አደጋ ሲታይ “አዝጋሚ” የሚባለው አቅጣጫ “ጅብ ከሄደ ውሻ ጮኸ” የሚያሰኝ እንዳይሆን ስጋት ይገባናል።
    ቀደም ብሎ እንደተጠቀሰው አደጋዎቹ መታየት ጀምረዋል። አንዳንዶቹ ደንድነዋል። ችግሮቹ በረጅም ዘመን የተጠራቀሙ እንደመሆናቸውም በረጅም ሒደት ብቻ ይፈቱ ቢባል በእነዚሁ ችግሮች ተጠልፎ እመንገድ መቅረት ይኖራል። በጠቅላይ ቤተ ክህነቱም፣ በአጥቢያም የሚቀርቡ ሐሳቦች እየተኮላሹ የሚቀሩት በዚሁ በተደላደለው በሽታ እየተጠለፉ ነው። (“አብዮት” የሚለውን ቃል ከደም መፋሰስ ወይም ከዓመጻ ጋራ እንዳይያያዝብን እንማጸናለን። “ሥር ነቀል” የሚለውን ቃል መጠቀም አልፈቀድንም። ችግር ችግሩን ብቻ እየመረጠ የሚነቅል ከሆነ እንኳን ባልከፋ።)

    ....በሚቀጥለው ገጽ ይቀጥላል....

    ReplyDelete
  5. ...ካለፈው ገጽ የቀጠለ....

    እኛ እንደምንለው፣ ቤተ ክርስቲያን የአሥር ዓመት መሠረታዊ የለውጥ እንቅስቃሴ ወይም አብዮት መጀመር ይገባታል። አብዮት በሚለው ፈንታ ሌላም ስም መስጠት ይቻላል። ዘገምተኛ ለውጥ የሚሉት ሰዎች በዚህ ከተስማሙ እኛ ከስሙ ቅሬታ የለንም። ነገር ግን በአዝጋሚ አካሄድ ከተባሉት ችግሮች በ10 ዓመት ሩቡን እንኳን መፍታት አይቻልም። ስለዚህ አብዮታዊ ወይም መሠረታዊ እና ፈጣን ለውጥ ይሻላል። ለውጡ ፈጣን መሆን የሚገባው በምን ምክንያት ነው?
    ሀ. በቤተ ክርስቲያን ላይ የተጋረጡት አደጋዎች እየተፈጸሙ፣ በብዛትም፣ በዓይነትም፣ በሚያስከትሉት ውጤትም እየጨመሩ
    መምጣታቸው በገሐድ መታየት በመጀመሩ፤
    ለ. ችግሮቹ እርስ በርስ የሚመጋገቡና የሚደጋገፉ በመሆናቸው፣ አንዱን ሳይነኩ ሌላውን ማቡካት ትርፉ ድካም ስለሆነ እንዲሁም፣
    ሐ. አሁን የተንሰራፋው ሥርዓት ብልሹ ቢሆንም ተቋርቋሪዎች እንደማያጣ በመረዳት፤ ለእነዚህ ተቆርቋሪዎች ረጅም ጊዜ መስጠት ለውጡን ያለጥርጥር ስለሚያደናቅፍ ነው።
    ከችግሮቹ መጠን አኳያ 10 ዓመት ብዙ አይደለም። ለውጡ አብዮታዊ እንዲባል የተመረጠበትም ምክንያት ከጊዜው ይልቅ በሂደቱ የማይመለስ መሆን እና በሚፈልገው መንፈሳዊ ቆራጥነት ነው። በጥበብ፣ በማስተዋል፣ ነገር ግን በተቻለ ሰብዓዊ ፍጥነት መጓዝ ይጠይቃል። የቀረውን ደሞ ለቤቱ ከእኛ በላይ ቀናዒ የሆነው አምላካችን ይሞላልናል።
    ይህንንስ አልን፤ “በ10 ዓመት ምን ምን ይሠራ?” የሚል ጥያቄ ይኖራል። እኛ ነገሩን ሁሉ ማወቅ አይቻለንም። እናውቃለን ብንልም እየዋሸን ነው። ይልቅ አንኳር አንኳር ጥቆማዎች እንስጥ።
    የ10 ዓመት ለውጥ አመላካቾች
    1. በመጀመሪያው ዓመት የሲኖዶስ ጉባኤ በጉዳዩ ላይ መክሮ፤ አንድ የለውጥ ጉባኤ ኮሚቴ ይሰይም።
    2. ይህ ኮሚቴ ከአራት ወር ባልበለጠ ጊዜ የቤተ ክህነቱ ተቀጣሪ ያልሆኑ ነጻ ባለሙያዎች ብቻ የሚገኙበት፣ ከ10 የማይበልጡ ሰዎች ያሉበት የጥናት ኮሚቴ ያቋቁም። ለኮሚቴውም የሚያስፈልገውን ያህል ገንዘብ፣ ያለምንም ስስት፣ ጠቀም ያለ በጀት ይመደብለት። ይህ የጥናት ኮሚቴ ምን ምን እንደሚሠራ በዝርዝር በጽሑፍ ይሰጠው። በአጠቃላይ ሥራው ያለውን ችግር ዘርዝሮ፣ በክፍል በክፍል ተንትኖ ማቅረብ ነው። ከዚሁም ጋራ የመፍትሔ አማራጮችን ያቀርባል። ይህንንም የሚያደርገው በሳይንሳዊ የጥናት ዘዴዎች፣ መረጃ ሰብሳቢዎችን አሰማርቶ፣ ተንታኞችን ቀጥሮ፣ ለመፍትሔ አማራጮች ወጥቶ ወርዶ (ካስፈለገው ሌላም አገር ተጉዞ) ይሆናል። እዚህ ውስጥ ማንኛውም የቅ/ ሲኖዶስ አባል ወይም የቤተ ክርስቲያን ሠራተኛ ለአስረጅነት ካልሆነ በኮሚቴ አባልነት ባይገባ ጥሩ ነው እንላለን። በመረጃ ስብሰባውና ትንተናው የተማሩ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ተሳትፎ ብዙ ይጠቅማል። ይህ የጥናት ኮሚቴ ሦስት ወራት ለዝግጅት፣ ከ8-12 ወራት ለዋናው ሥራ ይሰጠው።
    3. የጥናት ጉባኤው ውጤቱን ለውይይት ያቀርባል። ውይይቱም በየደረጃው የሚካሄድ ይሆናል። በሁሉም አጥቢያ ማድረግ የማይቻልም የማያስፈልግም ይሆናል። ከካህናት፣ ከአብነት መምህራን፣ ከገዳማውያን፣ ከመንፈሳዊ ኮሌጅ ተማሪዎችና መምህራን፣ ከሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች፣ ከተለያዩ ማኅበራት ጋራ በተናጠልም በጋራም በጥናቱ ላይ ተወያይቶ ሐሳቦችን ማዳበር።
    4. የጥናት ጉባኤው በውይይቶቹ የተገኙትን ነጥቦች አጠቃሎ ተንትኖ ከጥናቱ ጋራ በአባሪነት ያስቀምጣል። ከጥናቱና ከውይይቶቹ በመነሣትም የመጨረሻ የውሳኔ ሐሳቦችን ከአማራጮች ጋራ ያቀርባል። ይህም ከየአኅጉረ ስብከት የሚውጣጡ ተካፋዮችና ሁሉም ብፁዓን አበው በሚገኙበት የመጨረሻ ውይይት ይካሄድበታል። ብፁዓን አበው በዚህ ጉባኤ እንዲገኙ የሚገባው የጥናቱን ግኝት እንዲሰሙና ለመጨረሻ ውሳኔያቸው እንዲያግዛቸው ነው።
    5. በመጨረሻ ጉዳዩ ለውሳኔ ለቅዱስ ሲኖዶስ ይቀርባል። ጉባኤው ውሳኔ ከማሳለፉ በፊት በጋራ ለሦስት ቀን ሱባኤ ይይዛል። ከዚያም የመፍትሔ አማራጮቹን አስቀምጦ ወደ ቀጣዩ የተግባር እንቅስቃሴ ይገባል።
    6. በተመረጡት አማራጮች መሠረት አዲሱን ሂደት የሚመራ፣ የሚቆጣጠር ሙሉ ሥልጣን ያለው ጊዜያዊ አካል ይቋቋማል። ይኸው አካል ከአንድ ዓመት ያልበለጠ የትግበራ ዝግጅት፣ ጊዜና በጀት ይሰጠዋል። በዚህም ጊዜ ሕጎችን የመከለስና አዳዲሶቹን የማዘጋጀት፣ አወቃቀሮችን የመፈተሽና የመቀየር/ የማሻሻል ሥራ ያከናውናል፤ ሙከራ የሚደረግባቸውን አጥቢያዎች፣ አኅጉረ ስብከት ይመርጣል፤ በጀቱን አቅርቦ ያጸድቃል። በውስጣዊ አሠራርና ሕግ ሳይሆን በሌሎች አማራጮች የሚፈቱ ችግሮችን ለምሳሌ የተለያዩ አባቶችን የማስታረቅ፣ ከመንግሥትና ከሌሎች አካሎች ጋራ ያለውን ግንኙነት የሚመለከቱ አካሄዶችን አርቅቆ ለጳጳሳቱ የለውጥ ጉባኤ ያቀርባል። እርሱም በተራው ለሲኖዶሱ እያቀረበ ሂደቱ ይቀጥላል።
    7. የሙከራ ትግበራው ከ6-9 ወራት ተካሂዶ፤ በገለልተኛ ወገን ግምገማ ይደረጋል። ከግምገማው ውጤት በመነሣት በሕጎቹ፣ በአሠራሮቹ ወዘተ ላይ ማስተካከያ ተደርጎ ሪፖርት ይቀርባል። ከዚህ በመነሣት ቅዱስ ሲኖዶሱ በሕጎቹና አሠራሮቹ ላይ መክሮ ያጸድቃቸዋል፤ የሥራ መመሪያም ይሆናሉ።
    8. በአዲሶቹ አመለካከቶች፣ ሕጎች፣ አሠራሮች ላይ በየደረጃው በየክፍሉ ሥልጠና ይሰጣል። ጊዜያዊ አካሉም የሥራውን ሪፖርት አቅርቦ፣ ቀጣይ ሥራዎቹን ለሚመለከታቸው አካላት አስረክቦ ይሰናበታል፣ ይበተናል።
    9. በአምስተኛው ዓመት በሁሉም አኅጉረ ስብከትና የወረዳ ቤተ ክህነት ደረጃ አዲሱ አሠራር ሙሉ በሙሉ ተግባር ላይ መዋል ይጀምራል። ይህ ዓመት ከሞላ ጎደል የሙከራ ጊዜ ነው የሚሆነው። ሌሎቹ የቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋማትም በየፊናቸው የየራሳቸውን አዲስ አሠራር እንዲሁ ይጀምራሉ። በዓመቱ መጨረሻ ተቋማቱ በአዲሱ አሠራር ላይ ሪፖርታቸውን ያቀርባሉ። ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሪፖርቱን መርምሮ የቀጣዩን አምስት ዓመት አፈጻጸም ዕቅድ ይነድፋል። ሁለተኛው አምስት ዓመት/ ምዕራፍ አሁን ያለው ብልሹ አሠራር ከሥሩ መነቀል የሚጀምርበት ነው። ከፍተኛ ትግስት፣ ጥበብና ጽናት ይፈልጋል። ወሬው ወደ ተግባር የሚቀየርበት ስለሚሆን ውጊያውም ያይላል።
    10. በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት ቤተ ክርስቲያናችን በአስተዳደራዊና በመንፈሳዊ ቁመናው ወደ አዲስ ምዕራፍ የምትሸጋገርበትን ዘመን በቁርጠኝነት ለመቀበል የምትዝጋጅበት ነው።
    ይህ አሥር ዓመት ለብዙ ሰዎች በጣም ረጅም እንደሚመስል እናውቃለን። ነገር ግን ሥራ ከተሠራባቸው ረጅም አይደሉም። እጅግ ቀርፋፋ የሆነ አስተሳሰብና አሠራር ለረጅም ዘመናት በሰፈነበት ተቋም ውስጥ መሠረታዊ ለውጥ ለመጀመር ከዚህ ያጠረ ጊዜ የሚበቃ አይመስለንም። ከዚህ ባጠረ ጊዜ (ዋናው ጊዜ የመጀመሪያው አምስት ዓመት ነው) የቤተ ክርስቲያኒቱን ሁለንተናዊ ሕይወት የሚነካ መሠረታዊ ለውጥ መጀመር ከተቻለ ደስታችን ነው።
    እንግዲህ እኛ ያለንን አካፈልን። አንዳች የሚረባ ነገር እንዳለበት ከእኛ በተሻሉ ሰዎች ልብ ያድርና ለፍሬ ይበቃል። የደካማ ሰዎች ከንቱ ጩኸት ከሆነም እንዲሁ ይቀራል። ለቤተ ክርስቲያን ይበጃል የምንለውን በማስተዋል የምንነጋገርበትና የምንፈጽምበት የመንፈስ ቆራጥነት ካለን ይህን ዘመን እንሻገረዋለን። በያዝነው መንገድ ከቀጠልን ግን የዛሬ አምስት ዓመት የምንነጋገርው ከአሁኑ በባሰ አዘቅት ውስጥ ሆነን እንደሚሆን ለመገመት ነቢይነት አይጠይቅም።
    የአባቶቻችን አምላክ ይርዳን። አሜን።

    ReplyDelete
  6. Saturday, December 15, 2012ሰላም የሚፈጠረው ሰላም ብሎ በመነሳት ብቻ ነው።
    ሰላም የሚፈጠረው ሰላም ብሎ በመነሳት ብቻ ነው።
    ሁሉንም ቻይ አምላክ እንደየሥራችን የእጃችንን ይከፍለናል ማለት እውነት መሆኑ ባይካድም ምሕረቱ የማያልቅበት እየሱስ ክርስቶስ አብሮት የተሰቀለውን ነፍሰ ገዳይ እንደማረ ሁሉ እኛንም በምሕረቱ ይዳስሰናል ብለን እናምናለን። ደካሞች ነንና ጥንካሬን፣ ፈሪዎች ነንና ድፍረትን፣ ንፉግ ነንና ቸርነትን፣ ቂመኞች ነንና ይቅርታን፣ ከሀዲዎች ነንና እምነትን፣ እንደሚቸረን ደግሞ ደጋግሞ የተነገር በመሆኑ የቃሉ ፍጻሜ ላይ መጠራጠር ከሌለ በስተቀር ይሆናል ያለው እንደሚሆን በሙሉ እምነት መናገር ይቻላል።
    አዞ አፉን ከፍቶ በመተኛቱ የሞተ እየመሰላቸው የሚጠጉትን እንደሚያድን ሁሉ የፈጣሪን አምላክነት የሚፈታተኑትን በመንግሥቱ ቀናዊ ነውና እንደሚገስጻቸው ደግሞ ለዘመናት ያየነው ያስተዋልነው በመጽሐፍ ያነበብነው ነው።
    ይህንን ካልን በኋላ ሰሞኑን በዚህ በዳላስ የተደረገውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የሰላም ጉባኤ በጉጉት ከጠበቁትና በመጨረሻም በውጤቱ ከተበሳጩት መሃል እራሳቻንን እንደምራለን። ሰላም ወረደ ማለት የሁሉም ጊዜ እምነትን በማስፋፋትና በማጠናከር ላይ እንጂ በማፍረስ ላይ አይሆንም ከሚል አመለካከት። የመንፈሳዊ አባቶች ሱባኤና ጸሎት፣ የምእመናን ለቅሶና እግዚኦታ ምላሽ ያገኝ ይሆናል ከሚልም መንደርደሪያ በመነሳት ነበር።
    ለምን አልሆነም ለሚለው የበኩላችንን መናገር እንችላለን። ዋንኛውና የማንጣላበት ግን እሱ ስላልፈቀደ ብቻ ነው። ከሃገር ቤት የመጡ አባቶች ግዝትን አንስተው እዚህ ያሉትን መንፈሳዊ አባቶች ስልጣን ተቀብለው ከነክብራቸውና ከነማእረጋቸው እንዲገቡ መስማማታቸውን ሲቀበሉ፣ በስደት ያሉ መንፈሳዊ አባቶች ግን ለ 20 ዓመት ሲያነሱት የኖሩትን የመንበረ ስልጣን ጥያቄ አሁንም የሙጥኝ ማለታቸው ግን ሁላችንንም አሳዝኖናል።
    ክርስቶስ እንደሚገደል እያወቀ ወደ መሰቀያው የሄደው እኮ መሰወር አቅቶት አልነበረም። የሰቀሉትን ግፈኞች የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው ያለው መቅጣት ተስኖት አልነበረም። የተሰቀለው በደሙ ከሃጥያታችን ሊያነጻን ይቅር ያለው ምህረትን ሊያስተምረን ነው እንጂ። ለሐዋርያት ስልጣን የሰጠውም እንደኔ ሆናችሁ አስተምሩ በስሜ ወንጌልን ስበኩ ህሙማንን ፈውሱ አርአያም ሁኑ በማለት ነው። ታዲያ አባቶች ለዚህ መንፈሳዊ ስልጣን ያበቃቸውን አምላክ በተሰበጣጠረው ምእመን ችግር መፍትሄ እንጂ መለያያ ባይሆኑ እንዴት መልካም ነበር። መቼም እድሜ የማይደበቅ ስጦታ ነውና ለመጠራት የቀረን ስንት ጊዜ ይሆን ብሎ መጠየቅም መልካም ነው። ሰላምን ለሚፈልግ ምእመን ሰላም ለክሙ ማለት እንጂ መለያየትን እንዴት ለማሳለፍ ይፈለጋል። ተአምር የሚገለጽባቸው ገዳማት ደግሞ ያሉት ሃገር ቤት ነው ብለን እንቀበላለን። ያ የሆነው በየጥሻው በየዋሻው፣ በየሰቀላው፣ በየዱር ገደሉ ተጠልለው በሚጸልዩ መነኮሳትና አበው እንደሆነ እናምናለን።
    ስለሆነም ዛላለማዊ ስፍራን እንጂ ጊዚያዊ ወንበርን በመተው ለሰላም እንዲነሱ እንለምናለን።

    ReplyDelete

  7. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ምዕመናን ዓለም አቀፍ ማሕበር
    WORLD ASSOCIATION OF PARISHIONERS OF E.O.T. CHURCH
    ቁጥር፡ዐሰ2/212/05__________
    ቀን፡_27/1/2005____________
    ግልጽ ደብዳቤ
    “የትዕግሥት እና የመጽናናት አምላክ እግዚአብሔር እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ ፈቃድ
    እርስ በእርሳችን አንድ ሐሣብ መሆንን ይስጠን። ሁላችን አንድ ሆነን በአንድ አፍ በጌታችን
    በኢየሱስ ክርስቶስ እግዚአብሄርን እናመሰግነው ዘንድ።” ሮሜ 15:51
    ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ
    ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ወፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ
    ዋሽንግተን ዲ.ሲ.
    ለብፁዕ አቡነ ናትናኤል
    አቃቤ መንበረ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ እና
    የአርሲ አገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ
    አዲስ አበባ
    ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
    ካህናት እና ምዕመናን
    በያሉበት
    ዋና ጽሕፈት ቤቱን በዩናይተድ ስቴትስ ኦፍ አሜሪካ አድርጎ የተቋቋመው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምዕመናን ዓለም አቀፍ ማኅበር፤ ከሁሉ በማስቀደም፤ የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖትን ነፍስ ሁሉን አድራጊ የሆነው ፈጣሪያችን እግዚአብሔር ከቅዱሳኑ ጋር ያሳርፋት ዘንድ ያለውን ጽኑ ምኞቱን ይገልጣል።
    በመቀጠልም፤ በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ የተከሰተው መከፋፈል ይበልጥ እየተውሰበሰበ በመሄድ ላይ የሚገኘው በውግዘቱ ምክንያት መሆኑን አመልክተን ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ወፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ እና ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ወፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ ጽፈነው የነበረውን ደብዳቤ ማስታወስ ይፈቀድልን።
    ቅዱስነቶቻቸው ፈቃዳቸው ሆኖ በሰጡን ቀጠሮዎች የወከልናቸው የማኅበራችን አባላት ከሁለቱም ቅድሳን አባቶች ጋር በአካል ተገናኝተው ደብዳቤውን ከማቅረባቸውም ባሻገር፤ ጉዳዩን በቃል ጭምር እንዲያስረዱ ዕድል ተሰጥቷቸው ነበር። በዚያ ደብዳቤያችን አማካይነት፦
    ሀ. የቤተ ክርስቲያኗን ምዕመናን ከገጠሙን ዘርፈ ብዙ ፈተናዎች ሁሉ እጅግ
    የሚያሳስበን፤ አንድ ከሚያደርጉን ይልቅ የሚከፋፍሉን ነገሮች እየጨመሩና
    እየተውሰበሰቡ በመሄድ ላይ መገኘታቸውን፤
    ለ. ሐዋርያዊት፤ጥንታዊት፤ታሪካዊት፤ብሔራዊት እና ሲኖዶሳዊት የሆነችው
    ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን፤ አንድነቷን የተፈታተኑ ችግሮችን እየፈታች እና
    ዶግማዋን፤ ቀኖናዋን እና ሥርዓቷን እየጠበቀች፤ የደነገገቻቸውንም ሕጎች
    አክብራ እያስከበረች እስካሁኑ ትውልድ መዝለቅ መቻሏን፤

    ሐ. በአሁኑ ዘመን ግን፤ በአገር ውስጥ እና በውጭው ዓለም የሚገኙት ቅዱሳን
    እና ብፁዓን አባቶቻችን ከመለያየት አልፈው እስከ መወጋገዝ በመድረሳቸው፤
    ሥርዓታቷ እና ሕግጋቷ እየተጣሱ ታሪካዊ እንድነቷ ሊፈርስ በሚችልበት አደገኛ
    ጐዳና ስታዘግም መስተዋሏን፤ እና

    መ. ሌሎች ተዛማጅ ችግሮችንም በመዘርዝር፤ ከቤተ ክርስቲያናችን ችግሮች ሁሉ
    የውግዘቱ ጉዳይ ልዮ ትኩረት ተሰጥቶት ውግዘቱ እንዲሻርልን እና በየአካባቢያችን
    በሚገኙት እና ወደፊትም በሚመደቡት ብፁዓን አባቶች፤ ጐራ ሳንለይ መባረክ እና
    መመራት የምንችልባት ዕለት እንድትብትልን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስን
    እና ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስን ለምነን ነበር።

    ለዚህ ደብዳቤያችን በጎ ምላሽ እናገኝ ዘንድ እየፀለይን የተወሰኑ ወራት ካሳለፍን በኋላ፤ ባላሰብነው እና ባልጠበቅነው ሁኔታ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ክዚህ ዓለም በድንገት መለየታቸውን ተረድተን ደንግጠናል። አዝነናል። እንደየአቅማችንም ለቅዱስነታቸው ነፍስ ፀልየናል። የቅድሱነታቸውን ዕረፍት ተከትሎ ኢትዮጵያን በፕሬዚዳንትነት እና በጠቅላይ ሚኒስትርነት ለ21 ዓመታት የመሩትን የክቡር አቶ መለስ ዜናዊን ህልፈተ ህይወት ስለሰማን፤ ሐዘኑ ጋብ እስኪል ድረስ ይህንን ደብዳቤያችንን ለማዘግየት ተገድደን ጠብቀናል።

    በዚሁ ጊዜ ውስጥ ግን፤ በአገራችን ውስጥም ሆነ ከአገራችን ውጭ የሚገኙት አባቶቻችን ለቤተ ክርስቲያኗ ሰላም
    እና አንድነት ቅድሚያ ትኩረት ሰጥተው በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ዋናውን የአመራር ችግሯን ለመፍታት ቆራጥ
    አቋም ይዘው በመፀለይ ላይ መሆናችውን ስለተረዳን በእጅጉ ተጽናንተናል።

    ቤተ ክርስቲያናችን አገራዊ እንደ መሆኗ መጠን፤ በአገራችን ውስጥ የሚከሰቱ ማኅበራዊ፤ ፖለቲካዊ፤ ኤኰኖሚያዊ እና ባህላዊ ዕውንታዎች ሁሉ በቤተ ክርስቲያኗ ላይ የየበኩላቸውን አዎንታዊም ሆኑ አሉታዊ ተጽእኖዎች እንደሚያሳድሩ ከሩቁም ሆነ ከቅርቡ ታሪካችን እንረዳለን።

    የቤተ ክርስቲያናችንን ችግሮች ለመፍታት መንፈሳዊ አባቶቻችን በትዕግሥት፤ በአርቆ አስተዋይነት፤ በቅንነት እና በዕውነተኛነት ቆርጠው እስከተነሱ ድረስ፤ እግዚአብሔርም ስለሚጨመርበት፤የሚሳናቸው ነገር ይኖራል ብለን አንጠራጠርም።

    በቤተ ክርስቲያናችን ላይ የተጋረጠው ችግር በተለያዩ የታሪክ ወቅቶች የኦርየንታልንም ሆነ የምሥራቅን ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስትያናት እንደተፈታተነና በሂደትም መፍትሔ እንደተገኘለት ከአባቶቻችን የተሰወረ አይደለም።

    ፋሽስት ጣልያን አገራችንን በወረረችበት ዘመን ተከስቶ የነበረው የሰላም እና አንድነት ችግር እና የችግሩ አፈታት የቤተ ክርስቲያናችን ታሪክ አካል ስለሆነ በመጠኑም ቢሆን የመፍትሔ ሐሳብ ሊጠቁም ይችላል ብለን እንገምታለን።

    በአገር ውስጥም ሆነ ከአገር ውጭ የሚገኙት የመንፈስ ቅዱስ አባቶቻችን የሚመሩት ሐዋርያት በሠሩት ቀኖና እንደ መሆኑ መጠን፤ በመካከላቸው ሰላም እና አንድነትን ለማስፈን የሚያደርጉት ጥረት፤ ሐዋርያት በደነገጉት ቀኖና መሰረት እስከ ተከናወነ ድረስ የበረታ እንቅፋት ይገጥመዋል ብሎ መስጋት አይቻልም።

    ....በሚቀጥለው ገጽ ይቀጥላል...

    ReplyDelete
  8. ....ካለፈው ገጽ የቀጠለ...



    በተጨማሪም፤ ከማናቸውም ሌላ ስሜት ይልቅ በፍጹም መንፈሳዊ አመለካከት ጸንቶ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የአንድነት ችግር በአገራችን የፍትሐ ብሔር ሕግ ቁጥር 398 እና 399 ባገኘችው መብትና ሕጋዊ ሰውነት፤ በፍትሐ ነገሥቱ አንቅጽ 14 ንዑስ አንቀጽ 77 እና 78 በተደነገገው ሥርዓት እና እንደዚሁም ቅዱስ ሲኖዶስ ባወጣው ሕገ ቤተ ክርስቲያን ላይ ተመሥርቶ እና ችግሩንም ከተጨባጭ መረጃዎች ጋር አገናዝቦ መፍትሔ መሻቱ፤ ፍትሓዊ እና አዛላቂ ድምዳሜ ላይ ለመድረስ ይረዳል ብለን እናምናለን።

    ጉዳዩ አሳስቦን እላይ በጠቀስናቸው እና በሌሎች ተዛማጅ ሁኔታዎችም ላይ ሐሣብ ስንለዋወጥ ከቆየን በኋላ፤ የተገለጡልንን ፍሬ ነገሮች ለመንፈሳዊ አባቶቻችን ማሳወቅ ይገባናል ብለን ስለአመንን፤ ከዚህ በታች የዘረዘርናቸውን ሐሳቦች በታላቅ አክብሮት እናቀርባለን።

    1. ለሰላም እና አንድነቱ ችግር ፍቺ የሚቋጠረው ሐሣብ፤ የቤተ ክርስቲያኗን ደህንነት
    አስቀድሞ፤ ለወደፊቱ ተመሳሳይ ችግር እንዳይገጥማት ፅኑ መሠረት የሚጥል ቢሆን፤

    2. አገር ውስጥ እና ከአገር ውጭ የሚገኙት አባቶቻችን የቤተ ክርስቲያናችንን አንድነት
    ለማደስ የሚያደርጉት ጥረት ይቀል ዘንድ፤ አለ አንዳች ቅድመ ሁኔታ ውግዘቱ ቅድሚያ ተሰጥቶት ቢነሳ፤

    3. ለሰላም እና አንድነቱ ችግር አስተማማኝ መፍትሔ እስኪገኝ ድረስ በአገር ውስጥ
    የሚገኘው ቅዱስ ሲኖዶስ አዲስ ፓትርያርክ ከመምረጥ ቢታገስ፤

    4. ከቤተ ክርስቲያን ሰላም እና አንድነት የበለጠ ጉዳይ ስለሌለ፤ እግዚአብሔር በሰጠው
    ዕድል ተጠቅሞ አራተኛውን ፕትርያርክ ወደ መንበረ ተክለሃይማኖት የመመለሱ ጉዳይ ትኩረት ቢያገኝ፤

    5. የአራተኛውን ፕትርያርክ እድሜ እና አጠቃላይ ሁኔታ እግምት ውስጥ በማስገባት፤ በእሳቸው እና በቅዱስ ሲኖዶሱ ምርጫ በዕምነቱ፤ በዕውቀቱ እና በሥራ ልምዱ ብቃት
    ያለው አባት በእንደራሴነት መድቦ የአስተዳደር ተግባራትን ማካሄድ የሚቻልበት ሁኔታ
    ቢፈጠር፤

    6. ስለአራተኛው ፓትርያርክ ወደ ቀድሞ መንበራቸው መመለስ እና ከተመለሱ በኋላም
    ስለሚኖረው አሠራር በስደት የሚገኙት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ እና በእሳቸው የሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ ድርሻ ተግባራቸውን ቢፈጽሙ፤

    7. የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. መንግሥት ለአራተኛው ፓትርያርክ ወደ መንበራችው መመለስ ይሁንታ
    ቢሰጥ እና ተመልሰው በመንበረ ተክለ ሃይማኖት ይቀመጡ ዘንድም አስፈላጊውን ድጋፍ እና ትብብር ቢያደርግ፤ እና

    8. በአገር ውስጥም ሆነ ከአገር ውጭ የሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ካህናት እና ምዕመናን ለእርቀ ሰላሙ ውጤታማነት የሚጠበቅባቸውን
    ሁሉ በንቃት ቢያከናውኑ።

    በመጨረሻም፤ ይህን ግልጥ ድብዳቤያችንን መቋጨት የምንፈልገው፤ በሺህ ዓመታት የሚዘከር ታሪክ ያስመዘገበችው ቤተ ክርስቲያናችን ከአጠቃላዩ የኢትዮጵያ ሕዝብ ቁጥር ውስጥ የነበራት የመቶኛ ድርሻ እያሽቆለቆለ በመሄድ ላይ መገኘቱ የታላቅ ድክመት እና ችግር ምልክት መሆኑን በማሳሰብ ነው።

    ቸሩ ፈጣሪያችንን የተጣላው ታርቆ እና የተለያየው አንድ ሆኖ፤ በአሐቲ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ፤ በአንድ ቅዱስ ሲኖዶስ መንፈሳዊ አመራር ሥር ሆነን አንድ አምላከን የምናመልክበትን ቀን ያቀርብልን ዘንድ እንለምነዋለን።
    ወስብሃት ለእግዚአብሔር።

    ይሥሐቅ ክፍሌ ብርሃነማርቆስ ታደሰ
    የቦርዱ ሰብሳቢ ዋና ፀሐፊ

    ReplyDelete